ኢዴፓ አንድ ጠንካራ ተቃዋሚ ፓርቲ እንዲፈጠር ጠየቀ

 አዴፓ በሃገሪቱ አንድ ጠንካራ ተቃዋሚ ፓርቲ እንዲፈጠር ለተቃዋሚዎች፣ ለምሁራንና ለህዝቡ ጥያቄ ያቀረበ ሲሆን በሚቀጥሉት 6 ወራት ይህን ውጥን እውን ለማድረግ በትጋት እንደሚሰራም አስታውቋል፡፡ 
‹‹ጠንካራ ተቃዋሚ ፓርቲ መፍጠር የወቅቱ ቀዳሚና አንገብጋቢ ጥያቄ ነው›› በሚል ፓርቲው ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫ፤ ኢዴፓ የራሱን ጠቅላላ ጉባኤ ለማዘጋጀት ኮሚቴ አቋቁሞ እየተንቀሣቀሰ መሆኑን በመግለፅ ህዝቡ ድጋፉን እንዲሰጠው ጠይቋል፡፡ ‹‹ህዝቡ ባልተደራጀና ባልተቀናጀ ሁኔታ በሃይልና በነውጥ ጭምር እያደረገ ያለው እንቅስቃሴ የሚፈለገውን ለውጥ ሊያመጣ አይችልም›› ያለው ፓርቲው፤ ከዚህ ስጋት በመነሣት ኢዴፓ  ተቃዋሚ ፓርቲዎችና ምሁራን የህዝቡን ትግል በአግባቡ የሚመራ ጠንካራ ፓርቲ ለመፍጠር ተግተው መስራት አለባቸው ብሏል፡፡ 
ቀጣዮቹን 6 ወራት በመጠቀምም ፓርቲው ተጠናክሮ ሊመጣ የሚያስችለውን ጥረት ሁሉ እያደረገ መሆኑን በመግለፅ፤ የጉዳዩ ባለቤት የሆነው ህዝብ፣ መንግስትና ተቃዋሚ ፓርቲዎች ድጋፍ እንዲያደርጉለት ጠይቋል፡፡ 
መንግስት አንድ ጠንካራ ፓርቲ እንዲፈጠር ተገቢውን ድጋፍ ሊያደርግ ይገባል ያለው ኢዴፓ፤ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ውስጣዊ ድክመታቸውን በሃቅ በመገምገምና፣ ራሳቸውን በጥራት በማጠናከር፣ ከእርስ በእርስ መጠላለፍና መነቋቆር ወጥተው አንድ መሆን አለባቸው ብሏል፡፡
‹‹ኢዴፓ በዚህ አጀንዳ እውን መሆን የሚሠጠው ትኩረት ከፍተኛ ነው›› ያለው መግለጫው፤ የፓርቲን ደንብና መመሪያ እንዲሁም ፕሮግራም ከማሻሻል ጀምሮ የፓርቲውን ስያሜ እስከመቀየርና የተናጥል ህልውናውን እስከ ማክሰም የሚደርስ እርምጃ ለመውሠድ ዝግጁ መሆኑን ጠቁሟል፡፡ ይህን የሚያደርገውም አንድ ጠንካራ ተቃዋሚ ፓርቲ በመፍጠር መሆኑን የጠቀሰው ኢዴፓ፤ የሃገሪቱ ምሁራንም ዳር ቆመው ከመታዘብና ከመተቸት ፓርቲዎችን በእውቀታቸውና በገንዘባቸው እንዲደግፉ ጥሪ አቅርቧል፡፡ 
በሃገሪቱ የተፈጠረው የፖለቲካ ቀውስ ረግቦ እውነተኛ የብዙሃን ፓርቲ ስርአት የሚፈጠርበት ሁኔታ እንደሚኖር ፓርቲው ያለውን ተስፋ በመግለጫው አመላክቷል፡፡
source

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር